የልዩ ልዩ ወንጀል ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት

ይህ የስራ ክፍል ቀደም ሲል ለፍትሐብሔር እና ልዩ ልዩ ወንጀል ጉዳዮች ዘርፍ ተጠሪ ሆኖ የተደራጀ ሲሆን በአዲሱ አደረጃጀት ለጠቅላይ ዐቃቤ ህግ ዘርፍ ተጠሪ ሆኖ ተደራጅቷል፡፡ በዚህ ዳይሬክቶሬት ስር የሚታዩ ጉዳዮች ከፍሰት አንጻር ከፍተኛ መጠን ያላቸው በህብረተሰቡ ውስጥ በእለት ተእለት ደረጃ የሚፈጸሙ ወንጀሎች ሲሆኑ በዋናነት በወንጀል ህጉ የተደነገጉ የወንጀል ጉዳዮች ናቸው፡፡ 

ይህ የስራ ክፍል በስሩ የግድያ እና ከግድያ ጋር ተያያዥነት ያላቸው ወንጀል ጉዳዮች ዐቃቤ ሕግ ቡድን እና የልዩ ልዩ ወንጀል ጉዳዮች ዐቃቤ ሕግ ቡድን የሚገኙ ሲሆን ተግባር እና ኃላፊነቱም ከዚህ በታች እንደሚከተለው ሆኖ በዚህ የሥራ ክፍል ስር ክትትል የሚደረግባቸው ጉዳዮች በዋናነት በ1996 ዓ.ም በወጣው የወንጀል ሕግ ላይ የተዘረዘሩት ወንጀሎችን የሚመለከት እና በተለያዩ አዋጆች የተደነገጉ የወንጀል ጥፋቶች ሲሆኑ ከሙስና፣ ኢኮኖሚ፣ የተደራጁ እና ድንበር ተሸጋሪ እንዲሁም ሀገራዊ ደህንነትን የሚነኩ ወንጀሎች ውጪ ያሉ ጉዳዮችን የሚመለከት እና የሚከተሉት የልዩ ልዩ ወንጀል ጉዳዮች በዝርዝር የሚያካትት ይሆናል፡- 

  1. የተቋሙንና የዘርፉን ዕቅድ መነሻ በማድረግ የስራ ክፍሉን ተግባራት ያቅዳል፣ አፈፃጸማቸውን ይከታተላል ፣ድጋፍ ይሰጣል፤ 
  2. ስትራቴጂዎች፣ ፖሊሲዎችና ሕጎች ለመቅረጽ ግብዓት የሚሆኑ ምክረ ሀሳቦችን ያቀርባል፤ 
  3. ለስራ ክፍሉ የሚያስፈልገውን ሰብአዊ እና ቁሳዊ ግብአት እንዲሟላ ያደርጋል፣ ስራ ላይ መዋሉን ይከታተላል፤ 
  4. የስራ ክፍሉ ተግባራት የሚመሩበትን መመሪያዎች እንዲዘጋጁ ያደርጋል ፣ሲፀድቁም በአሰራሩ መሠረት መፈጸማቸውን ያረጋግጣል ፣ በየጊዜው እንዲሻሻሉ ሃሳብ ያቀርባል፤ 
  5. የመንግሰት ሰራተኞች የስራ ግዴታን በአግባቡ ባለመወጣት የሚፈጸም ወንጀል (የወንጀል ሕግ አንቀጽ 420-426)፤ 
  6. ሌሎች ሰዎች በመንግስት ስራ ላይ የሚፈጽሟቸው ወንጀሎች (የወንጀል ሕግ አንቀጽ 432-442)፤ 
  7. በፍትህ አስተዳደር ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች (የወንጀል ሕግ አንቀጽ 443-465)፤ 
  8. በህዝብ ደህንነት፣ ሰላምና ተረጋግቶ መኖር ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች (የወንጀል ሕግ አንቀጽ 477-480 እና489-493) ይሁን እንጂ ከሽብርተኛነት፣ ከማዘዋወርና ከመነገድ አላማ ወይም አደገኝነታቸው ለሚታወቁ ሰዎች የጦር መሳሪያን ማዘዋወር እና በሀገር ደህንነት ላይ የሚፈጸሙ ሌሎች ወንጀሎችን አይመለከትም፤ 
  9. በጤና ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች (የወንጀል ሕግ አንቀጽ 514-547) ከዚህ ጋር ተያይዞ የምግብና መድኃኒቶች ቁጥጥር አዋጅን በመጣስ የሚፈጸሙ ወንጀሎችን ያካትታል፤ (አደገኛ ዕጽ ዝውውር ጋር የተያያዙ የተደራጁ እና ድንበር ተሸጋሪ ወንጀል ዳይሬክቶሬት ስልጣን ከሆኑት ውጪ) 
  10. በሰው ህይወት፣ አካልና ጤንነት ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች (የወንጀል ሕግ አንቀጽ 539-579)፤ 
  11. በሰው ነጻነት ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች (የወንጀል ሕግ አንቀጽ 580-606)፤ 
  12. በክብር ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች (የወንጀል ሕግ አንቀጽ 613-619) 
  13. በመልካም ፀባይ ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች (በሴቶች እና በህጻናት ላይ ጾታን ወይም የእድሜ ህጻንነትን ምክንያት በማድረግ ከሚፈጸሙ የወንጀል ድርጊቶች ውጪ ያሉ) 
  14. በሰዎች የንብረት መብት ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች (ከ665-705፣ 713-715 እና 725-735) የሙስና ወንጀሎችን የሚመለከት አይሆንም 
  15. የደን ጥበቃ አዋጅን በመተላለፍ የሚፈጸም ወንጀል (አዋጅ ቁጥር 542/1999)፤ 
  16. የአካባቢ ጥበቃ አዋጅን በመተላለፍ የሚፈጸም ወንጀል (አዋጅ ቁጥር 299/1995፣ 300/1995)፤ 
  17. የተሽከርካሪዎች የሶስተኛ ወገን መድን ሽፋንን ለመደንገግ የወጣውን አዋጅ በመተላለፍ የሚፈጸም ወንጀል፣ 
  18. አዋጅ ቁጥር 384/1996ን በመተላለፍ የሚፈጸሙ ወንጀሎች፤ 
  19. የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት አዋጅ ቁጥር 621/2001ን በመተላለፍ የሚፈጸም ወንጀል፤ የሙስና ወንጀሎችን አይመለከትም 
  20. የሰንደቅ ዓላማ አዋጅ በመተላለፍ የሚፈጸም ወንጀል (አዋጅ ቁጥር 654/2001)፤ 
  21. የወንጀል ጠቋሚዎችና ምስክሮች ጥበቃ አዋጅን በመተላለፍ የሚፈጸም ወንጀል (አዋጅ ቁጥር 699/2002) እና በሌሎች አዋጆች የተመለከቱ ልዩ ልዩ ወንጀሎችን ይመለከታል፤ 
  22. ያለደረሰኝ ግብይት ወንጀሎች (ቀደም ሲል በኢኮኖሚ ወንጀል ጉዳዮች ስር ይታዩ የነበሩ ወንጀሎች) 
  23. በአዋጅ ቁጥር 813/2006 መሰረት የንግድ እቃዎችን ማከማቸት፣ የሸማቾች መብት ላይ የሚፈጸሙ ድርጊቶች፣ ከጥራት ደረጃ በታች የሆኑ ምርቶችን ለገበያ ማቅረብ እና የመሳሰሉት (በግልጽ ለኢኮኖሚ ወንጀል ጉዳዮች ከተሰጡት የንግድ አሰራር እና ሸማቾች መብት ጥበቃ አዋጅን በመተላለፍ ከሚፈጸሙ ወንጀሎች ውጪ ያሉ ወንጀሎች) 
  24. የቅጂ እና ተዛማች መብት ጥሰቶች፣ አነስተኛ ፈጠራ መብት ጥሰቶች፣ 
  25. በልዩ ልዩ ወንጀሎች የተገኘ ገንዘብ ወይም ንብረት ህጋዊ አስመስሎ ማቅረብ እና ስለመርዳት፣ 

❖ በሌሎች የወንጀል ጉዳዮች ዐቃቤ ሕግ የስራ ክፍሎች ከሚታዩ ሌሎች የወንጀል ጉዳዮች ጋር የልዩ ልዩ ወንጀል ጉዳዮች በተደራቢነት የሚገኝ በሚሆን ጊዜ ከፍተኛ ቅጣት የሚያስከትለው ጉዳይ የልዩ ልዩ ወንጀል ክሱ ሆኖ ሲገኝ በዚህ ዳይሬክቶሬት ተጠቃሎ ይታያል፡፡ 

❖ ከላይ በተጠቀሱት የወንጀል ጉዳዮች በፍርድ ቤት የተላለፈ የገንዘብ ቅጣትን በወንጀል ህጉ መሰረት የሚያስፈፅም ሆኖ 

በተጨማሪ ዳይሬክቶሬቱ ተግባር እና ኃላፊነት ይኖሩታል፡-

  1. በስራ ክፍሉ ያሉ ባለሙያዎችን የክህሎት ክፍተት ለይቶ አቅማቸው የሚገነባበትን ስልጠናና ትምህርት እንዲያገኙ ያደርጋል፤የስራ ክፍሉን ሰራተኞችን የስራ አፈፃፀም ይመዝናል፤ 
  2. ከዘርፉ ኃላፊ ጋር በመመካከር ለስራ ክፍሉ ተልእኮ መሳካት አስተዋፅኦ ካላቸው ተቋማትና የሥራ ክፍሎች ጋር የሥራ ግንኙነቶችን ይፈጥራል፣ በቅንጅት ይሰራል፤ 
  3. ከስራ ክፍሉ ተልእኮ ጋር የተያያዙ መረጃዎችን እና ምርጥ ተሞክሮዎችን ያደራጃል፣ 
  4. ለስራ ክፍሉ የሚቀርቡ አቤቱታዎችን እና ቅሬታዎችን ተቀብሎ ያስተናግዳል፣ ተገቢውን ምላሽ ይሰጣል፤ 
  5. የስራ ክፍሉን የስራ አፈፃፀም ይከታተላል፣ ይገመግማል፣ ከቡዱኖች ሪፖርት ይቀበላል ፣ ግብረ መልስ ይሰጣል፣ የስራ አፈጻጸም ሪፖርት አዘጋጅቶ በወቅቱ ለሚመለከታቸው አካላት ያቀርባል፣ 
  6. በስራ ክፍሉ ተልእኮ የኅብረተሰብ ክፍሎች የሚሳተፉበት የሕዝብ መድረክ ያዘጋጃል፣ያሳትፋል፣ 
  7. የዳይሬክቶሬቱ ሠራተኞች በተቀመጡ እሴቶች መሠረት በስነምግባር እና በባለቤትነት ስሜት እንዲሰሩ እና ውጤታማ እንዲሆኑ የኮቺንግ (Coaching) ሥራ ያከናውናል፣ በስራ ክፍሉ ያሉትን ሰራተኞች በስነምግባር እንዲገነቡ ያደርጋል፣ ጥሰት ሲፈፀም ተጠያቂነት እንዲሰፍን ያደርጋል፤ 

➢ የልዩ ልዩ ወንጀሎቹ አይነት እና የሚታዩበት ደረጃ 

ከላይ የተጠቀሱት ወንጀሎች በፈጻሚዎቻቸው ማንነት፣ በወንጀል አፈጻጸሙ ሁኔታ፣ በወቅታዊ አንገብጋቢነታቸው ደረጃ፣ በማስረጃ ረገድ በሚኖራቸው ውስብስብነት መሰረት በማድረግ ወንጀሎቹን በልዩ፣ ከባድ እና መደበኛ ደረጃ መለየት አስፈላጊ ይሆናል፡፡ 

በዚህም መሰረት በዳይክቶሬቱ አማካኝነት የሚታዩ ጉዳዮች፡- 

  1. ከላይ የተፈጸሙት ወንጀሎች በኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ጠቅላይ ሚኒስትር በቀጥታ የሚሾሙ፣ በኢ.ፌ.ዲ.ሪ. የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ወይም በምክር ቤቱ የሚሾሙ አመራሮች እና የክልል ምክር ቤት አባላት እና በምክር ቤቶቹ የሚሾሙ አመራሮች በሚሆንበት ወቅት፡ 
  2. በማስረጃ አሰባሰብ ውስብስብነታቸው እና የወንጀል ድርጊቱን በማስረጃ ለማረጋገጥ ከፍተኛ የሰው ሀይል፣ የባለሙያ ስብጥር እና የገንዘብ ሀብት የሚጠይቁ ጉዳዮች እና የዘርፉ ኃላፊ ጉዳዩ በማዕከል/ዳይሬክቶሬት እንዲያዝ መመሪያ ሲሰጥበት፤ 
  3. ሁለት ክልሎችን ወይም በአዲስ አበባ ያሉ ሁለት እና ከሁለት በላይ የከተማ አስተዳደር አካላት (ክፍለ ከተሞችን) የሚያነካካ የወንጀል ድርጊት በሚሆንበት ጊዜ፤ 
  4. በክብር ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች በሚሆኑበት ጊዜ ተበዳዩ በሚኒስቴር ወይም በኮሚሽነር ደረጃ ያለ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣን ከሆነ፣ 

❖ የተፈጸመው ወንጀል ከወቅታዊነቱ ጋር በተገናኘ ከፍተኛ የህዝብ ጥያቄ ያለበት እና መንግስትም በጥብቅ የሚከታተለው ጉዳይ ከሆነ እና የዘርፉ ኃላፊ ጉዳዩ በማዕከል/ዳይሬክቶሬት እንዲያዝ መመሪያ ሲሰጥበት፤ ከላይ የተዘረዘሩትን ሁኔታዎች የሚያሟሉ ወንጀሎች ደረጃቸው ከባድ ይሆናል፡፡ 

❖ ከላይ ከተገለጹት ውጪ ያሉት ወንጀሎች በደረጃቸው መደበኛ ሲሆኑ የሚታዩትም በመደበኛነት በጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ በክ/ከተማ ደረጃ በተቋቋሙት ጽ/ቤቶች በኩል ይሆናል፡፡ 

➢ በስራ ክፍሉ በማዕከል ደረጃ የሚታዩ የወንጀል ጉዳዮች ዝርዝር 

የስራ ሂደቱ በቅርንጫፍ ጽ/ቤት የሚታዩ የልዩ ልዩ ወንጀል ጉዳዮችን መከታተሉ እንደጠበቀ ሆኖ ራሱ በስራ ክፍሉ በማዕከል ደረጃ የሚያዙ ጉዳዮችን በመከታተል የሚሰራ ሲሆን በዚህም መሰረት በስራ ክፍሉ የሚታዩ ጉዳዮች፡- 

  1. የግድያ ወንጀል፣ ከግድያ ጋር የተያያዙ ወንጀሎች፤ 
  2. ከበርካታ ሰዎች ጋር ተያያዥነት ያላቸው ውስብስብ ወንጀሎች፣ 
  3. ጥቅም ለማግኘት ወይም ገንዘብ ለማግኘት ተብሎ የሚፈፀሙ የሰዎች ጠለፋ ወንጀል፣ 
  4. ከላይ በተጠቀሱት ወንጀሎች የተገኘ ገንዘብን ህጋዊ አስመስሎ ማቅረብ፣ 

➢ ልዩ ልዩ ወንጀሎችን በተመለከተ በጠቅላይ ዐ/ሕግ የአዲስ አበባ ከተማ ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች ደረጃ ክትትል የሚደረግባቸው የወንጀል ጉዳዮች 

ከዚህ በላይ በተመለከተው አግባብ ለዳይሬክቶሬቱ የተሰጠው የወንጀል ስልጣን እንደተጠበቀ ሆኖ በቅርንጫፍ ጽ/ቤት ደረጃ የሚታዩ የወንጀል ጉዳዮች የሚታዩበትን አግባብ እና የወንጀሎቹን ጠቅላላ ዝርዝር ቀርቧል፡- 

በዚህ መሰረት ልዩ ልዩ በሚል የተለዩት ወንጀሎች በቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች የሚታዩት፡- 

  1. በምርመራ ሂደታቸው ውስብስብ ያልሆኑ፣ 
  2. በወቅታዊነታቸው በአንድ ማዕከል መያዛቸው አስፈላጊ የማይሆኑ 
  3. በግልጽ ለዳይሬክቶሬቱ ያልተሰጡ ሌሎች ልዩ ልዩ የወንጀል ጉዳዮች ሲሆኑ 

❖ በጽ/ቤቶች ስልጣን ስር ከሚወድቁ ወንጀሎች ጋር በተያያዘ ህጋዊ ያልሆነ ገንዘብን ህጋዊ አስመስሎ የማቅረብ ወንጀሎች በቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች የሚታዩ ይሆናሉ፡፡ 

❖ በዳይሬክቶሬቱ እና በጽ/ቤት በሚታዩ ወንጀሎች ለወንጀሉ መፈጸሚያ የዋሉ ንብረቶችን ወይም ከወንጀሉ ፍሬ ሆነው የተገኙ ንብረቶችን በመከታተከል እና በመለየት በህጉ መሰረት እንዲከበር እንዲወረስ እና በወንጀሉ ምክንያት የጠፋ ሃብት ወይም የደረሰ ጉዳት ካለ እንዲካስ የማድረግ ሃላፊነትን በወንጀል የተገኘ ሀብት ማስመለስ ዳይሬክቶሬት ጋር በመተባበር የሚፈጸም ይሆናል፡፡ 

Department Lead

ሙላቱ ገቢሣ ሡፋ

ዳይሬክተር